SAʴý

እ. ኤ. አ. ታኅሣሥ 8/2015 የተከናወነ የምህረት ኢዮቤልዩ የቅዱስ በር የመክፈቻ ሥነ-ሥርዓት እ. ኤ. አ. ታኅሣሥ 8/2015 የተከናወነ የምህረት ኢዮቤልዩ የቅዱስ በር የመክፈቻ ሥነ-ሥርዓት 

ቫቲካን በኢዮቤልዩ ዓመት መጀመሪያ ላይ የሚከፈቱ ቅዱስ በሮችን በማስመልከት ማብራሪያ ሰጠ

በቅድስት መንበር ለሕዝቦች የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ማስፋፊያ ጳጳሳዊ ጽሕፈት ቤት የላቲን ሥርዓት በምትከተል ካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያን እንደ ጎርግሮሳውያኑ በመጭው 2025 የሚከበረውን የኢዮቤልዩ በዓል ዝግጅት በማስመልከት ማብራሪያ ሰጥቷል። ጳጳሳዊ ጽሕፈት ቤቱ በሮም የሚገኙ የአራት ባዚሊካዎች እነርሱም የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፣ የቅዱስ ጴጥሮስ፣ የቅዱስ ዮሐንስ ላተራን እና የቅዱስ ጳውሎስ ባዚሊካ በሮች እንዲሁም የአንድ ማረሚያ ቤት በር ብቻ ለመንፈሳዊ ነጋዲያን ክፍት ሆነው እንደሚቆዩ በማብራሪያው ገልጿል።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን

በሮሜ ምዕ. 5:5 ላይ “ተስፋ ቅር አያሰኝም” የሚለውን መሠረት በማድረግ ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ እንደ ጎርጎሮሳውያኑ በ 2025 ዓ. ም. ከሚከበረው የኢዮቤልዩ ዓመት ቀደም ብለው ባወጡት መመሪያ፥ የቅዱስ ጴጥሮስ ባዚሊካ እና የሌሎቹ ሦስት ባዚሊካዎች ማለትም ቅዱስ ዮሐንስ ላተራን፣ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም እና የቅዱስ ጳውሎስ ባዚሊካ ዋና በሮች እንደሚከፈቱ ገልጸው፥ ለታራሚዎች ያላቸውን ተጨባጭ ቅርበት ለመግለጽ የአንድ ማረሚያ ቤት በርን ለመክፈት ፍላጎት እንዳላቸው አስታውቀዋል።

በቅድስት መንበር ለሕዝቦች የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ማስፋፊያ ጳጳሳዊ ጽሕፈት ቤት ይህን በድጋሚ ያረጋገጠው፥ በዓለማችን የወንጌል ስርጭትን በተመለከተ የሚቀርቡ መሠረታዊ ጥያቄዎችን በማስታወስ ሐሙስ ሐምሌ 25/2016 ዓ. ም. ይፋ ባደረገው ማብራሪያ እንደሆነ ታውቋል።

ጳጳሳዊ ጽሕፈት ቤቱ በተለይ ከሮም ውጭ በሌሎች አካባቢዎች የሚገኙ ቤተ ክርስቲያኖች ቅዱስ በሮቻቸውን መከፈትን በተመለከተ መመሪያ አውጥቷል። እንደ ጎርጎሮሳውያኑ በ 2025 የሚከበረውን የኢዮቤልዩ ዓመት ከግምት ውስጥ በማስገባት፣ በሌሎች አካባቢዎች የሚገኙ ካቴድራሎች፣ በዓለም አቀፍ እና በብሔራዊ የንግደት ሥፍራዎች የሚገኙ ቤተ መቅደሶች በተለይ ጉልህ የአምልኮ ቦታዎች ቅዱስ በሮች የመክፈቻ በዓሉ መንፈሳዊ ሥነ-ሥርዓት አስመልክቶ ጥያቄዎች መቅረባቸውን አስታውሷል።

የቅዱስ ጴጥሮስ እና የርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ባዚሊካዎች
“ጥልቅ ምኞትን ሊገልጹ የሚችሉ ሐዋርያዊ የአምልኮ ተነሳሽነቶችን በጥንቃቄ እያጤንን፣ የርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ትክክለኛ መመሪያን ማስታወስ አስፈላጊ ነው” ሲል ጳጳሳዊ ጽሕፈት ቤቱ አስታውቋል።

ጽሕፈት ቤቱ በማብራሪያው፥ እንደ ጎርጎሮሳውያኑ ከ1300 የመጀመሪያው ልዩ የኢዩቤልዩ ዓመት ምልክት ጀምሮ የተላለፈውን የእግዚአብሔርን የምሕረት ሙላትን በምስጢረ ንስሐ፣ በበጎ አድራጎት እና በተስፋ በኩል ለሌሎች ማዳረስን የሚያግድ ነገር እንደሌለ አስረድቷል። ይህን ታሳቢ በማድረግ ምእመናን የጸጋ ጊዜን በሙላት ለመኖር የሚረዳ እና እንደ ጎርጎሮሳውያኑ በግንቦት 13/2024 በወጣው ሐዋርያዊ መመሪያ ውስጥ የተጠቀሱ መንፈሳዊ ሥፍራዎችን እና ልዩ የተግባር መንገዶች መረዳት እንደሚገባ ጽሕፈት ቤቱ አሳስቧል።

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ፥ ሐዋርያው ጳውሎስ ወደ ሮም ሰዎች በላከው መልዕክት ምዕ. 5:5 ላይ “ተስፋ ቅር አያሰኝም” የሚለውን በመጥቀስ ባሰላለፉት መመሪያ፥ የኢዮቤልዩ ዓመት እንደ ጎርጎሮሳውያኑ በ2024 የብርሃነ ልደቱ በዓል ዋዜማ በቅዱስ ጴጥሮስ ባዚሊካ ዋና በር የመክፈቻ ሥነ-ሥርዓት እንደሚጀመር አስታውቀዋል።

በቫቲካን የሚገኘው የቅዱስ ጴጥሮስ ባዚሊካ ቅዱስ በር በርዕሠ ሊቃነ ጳጳት የሚከፈተው በኢዮቤልዩ ዓመት መጀመሪያ ላይ ብቻ ሲሆን፥ ይህም የቅዱስ ዓመት መጀመሪያን ለማመልከት የሚከፈት የመጀመሪያው በር እንደሆነ ይታወቃል። የቅዱስ ጴጥሮስ ባዚሊካ በር በመንፈሳዊ የአምልኮ ሥነ-ሥርዓት ለመጀመሪያ ጊዜ የተከፈተው በቀድሞው ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት አሌክሳንደር ስድስተኛ ዘመን እንደ ጎርጎሮሳውያኑ በ 1500 ዓ. ም. እንደ ነበር ይታወሳል።

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ቀጥለውም እንደ ጎርጎርሳውያኑ በታኅሳስ 29/2024 ዓ. ም. በሮም የሚገኝ የቅዱስ ዮሐንስ ላተራን ባዚሊካ ቅዱስ በር እንደሚከፍቱት እና በዕለቱም የኢዩቤልዩ በዓልን ምክንያት በማድረግ በዓለም ዙሪያ በሚገኙ ካቴድራሎች ውስጥ በአካባቢው ጳጳስ የሚመራ የመስዋዕተ ቅዳሴ ጸሎት እንደሚቀርብ ታውቋል።

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ እንደ ጎርጎሮሳውያኑ እሑድ ጥር 1/2025 ዓ. ም. በሮም የሚገኝ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ባዚሊካ ቅዱስ በር በመክፈት የመስዋዕተ ቅዳሴ ጸሎት የሚያቀርቡ ሲሆን ቀጥሎም እንደ ጎርጎሮሳውያኑ እሑድ ጥር 5/2025 ዓ. ም. በበዓለ ጥምቀት ዋዜማ የቅዱስ ጳውሎስ ባዚሊካ ቅዱስ በር እንደሚከፍቱት ታውቋል።

ቅዱስነታቸው በመመሪያቸው “በዓመቱ ውስጥ ምዕመናን በእግዚአብሔር ጸጋ ላይ ባለው የተስፋ አዋጅ እና ውጤታማነታቸውን በሚያረጋግጡ ምልክቶች ላይ ሙሉ በሙሉ እንዲሳተፉ ለማድረግ ጥረት መደረግ አለበት” ሲሉ ጽፈዋል።

እንደ ጎርጎሮሳውያኑ ታህሳስ 28/2025 ዓ. ም. የኢዮቤልዩ በዓል በዓለም ዙሪያ ባሉ ቤተ ክርስቲያናት ዘንድ የሚያበቃበት ዕለት ሲሆን፥ በሮም በሚገኙ የቅዱስ ዮሐንስ ላተራን ፣ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም እና የቅዱስ ጳውሎስ ባዚሊካ በሮችም በተመሳሳይ ዕለት እንደሚዘጉ ታውቋል።

በመጨረሻም፣ የኢዮቤልዩ ዓመት እንደ ጎርጎሮሳውያኑ በጥር 6/2026 ዓ. ም. በሮም በሚከበረው የብርሃነ ጥምቀቱ መስዋዕተ ቅዳሴ ሥነ-ሥርዓት በይፋ እንደሚጠናቀቅ ታውቋል።

 

03 August 2024, 17:05